መዝሙር 1

1 ምስጉን ነው በክፉዎች ምክር ያልሄደ፥ በኃጢአተኞችም መንገድ ያልቆመ፥ በዋዘኞችም ወንበር ያልተቀመጠ።

2 ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለዋል፥ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል።

3 እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደ ተተከለች፥ ፍሬዋን በየጊዜዋ እንደምትሰጥ፥ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፤ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል።

4 ክፉዎች እንዲህ አይደሉም፥ ነገር ግን ነፋስ ጠርጎ እንደሚወስደው ትቢያ ናቸው።

5 ስለዚህ ክፉዎች በፍርድ፥ ኃጢአተኞችም በጻድቃን ማኅበር አይቆሙም።

6 እግዚአብሔር የጻድቃንን መንገድ ያውቃልና፥ የክፉዎች መንገድ ግን ትጠፋለች።

መዝሙር 2

1 አሕዛብ ለምን ያጕረመርማሉ? ወገኖችስ ለምን ከንቱን ይናገራሉ?

2 የምድር ነገሥታት ተነሡ፥ አለቆችም በእግዚአብሔርና በመሢሑ ላይ እንዲህ ሲሉ ተማከሩ።

3 ማሰርያቸውን እንበጥስ፥ ገመዳቸውንም ከእኛ እንጣል።

4 በሰማይ የሚኖር እርሱ ይሥቃል፥ ጌታም ይሣለቅባቸዋል።

5 በዚያን ጊዜ በቍጣው ይናገራቸዋል፥ በመዓቱም ያውካቸዋል።

6 እኔ ግን ንጉሤን ሾምሁ በተቀደሰው ተራራዬ በጽዮን ላይ።

7 ትእዛዙን እናገራለሁ፤ እግዚአብሔር አለኝ። አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ።

8 ለምነኝ፥ አሕዛብን ለርስትህ የምድርንም ዳርቻ ለግዛትህ እሰጥሃለሁ።

9 በብረት በትር ትጠብቃቸዋለህ፥ እንደ ሸክላ ሠሪ ዕቃዎች ትቀጠቅጣቸዋለህ።

10 አሁንም እናንት ነገሥታት፥ ልብ አድርጉ፤ እናንት የምድር ፈራጆችም፥ ተገሠጹ።

11 ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ፥ በረዓድም ደስ ይበላችሁ።

12 ተግሣጹን ተቀበሉ ጌታ እንዳይቈጣ እናንተም በመንገድ እንዳትጠፉ፥ ቍጣው ፈጥና ትነድዳለችና። በእርሱ የታመኑ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው።

መዝሙር 3

ከልጁ ከአቤሴሎም ፊት በሸሸ ጊዜ የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ የሚያስጨንቁኝ ምንኛ በዙ! በኔ ላይ የሚቆሙት ብዙ ናቸው።

2 ብዙ ሰዎች ነፍሴን። አምላክሽ አያድንሽም አልዋት።

3 አንተ ግን አቤቱ፥ መጠጊያዬ ነህ፥ ክብሬንና ራሴንም ከፍ ከፍ የምታደርገው አንተ ነህ።

4 በቃሌ ወደ እግዚአብሔር እጮሃለሁ ከተቀደሰ ተራራውም ይሰማኛል።

5 እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁም፤ እግዚአብሔርም ደግፎኛልና ነቃሁ።

6 ከሚከብቡኝ ከአእላፍ ሕዝብ አልፈራም።

7 ተነሥ፥ አቤቱ፤ አምላኬ ሆይ፥ አድነኝ፤ አንተ የጠላቶቼን መንጋጋ መትተሃልና፥ የክፉዎችንም ጥርስ ሰብረሃልና።

8 ማዳን የእግዚአብሔር ነው፥ በረከትህም በሕዝብህ ላይ ነው።

መዝሙር 4

ለመዘምራን አለቃ በበገናዎች፤ የዳዊት መዝሙር።

1 የጽድቄ አምላክ በጠራሁት ጊዜ መለሰልኝ፥ በጭንቀቴም አሰፋህልኝ፤ ማረኝ፥ ጸሎቴንም ስማ።

2 እናንት የሰው ልጆች፥ እስከ መቼ ድረስ ልባችሁን ታከብዳላችሁ?

3 እግዚአብሔር በጻድቁ እንደ ተገለጠ እወቁ፤ እግዚአብሔር ወደ እርሱ በተጣራሁ ጊዜ ይሰማኛል።

4 ተቈጡ፥ ነገር ግን ኃጢአትን አታድርጉ፤ በመኝታችሁ ሳላችሁ በልባችሁ አስቡ፤ ዝም በሉ።

5 የጽድቅን መሥዋዕት ሠዉ፥ በእግዚአብሔርም ታመኑ።

6 በጎውን ማን ያሳየናል? የሚሉ ብዙ ናቸው። አቤቱ፥ የፊትህ ብርሃን በላያችን ታወቀ።

7 በልቤ ደስታን ጨመርህ፤ ከስንዴ ፍሬና ከወይን ከዘይትም ይልቅ በዛ።

8 በሰላም እተኛለሁ አንቀላፋለሁም፤ አቤቱ፥ አንተ ብቻህን በእምነት አሳድረኸኛልና።

መዝሙር 5

ለመዘምራን አለቃ በዋሽንት፤ የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ ቃሌን አድምጥ፥ ጩኸቴንም አስተውል፤

2 የልመናዬን ቃል አድምጥ፥ ንጉሤና አምላኬ ሆይ፥ አቤቱ፥ ወደ አንተ እጸልያለሁና።

3 በማለዳ ድምፄን ትሰማለህ፥ በማለዳ በፊትህ እቆማለሁ፥ እጠብቃለሁም።

4 አንተ በደልን የማትወድድ አምላክ ነህና፤ ክፉ ከአንተ ጋር አያድርም።

5 በከንቱ የሚመኩ በዓይኖችህ ፊት አይኖሩም፤ ክፉ አድራጊዎችን ሁሉ ጠላህ።

6 ሐሰትን የሚናገሩትን ታጠፋቸዋለህ፤ ደም አፍሳሹንና ሸንጋዩን ሰው እግዚአብሔር ይጸየፋል።

7 እኔ ግን በምሕረትህ ብዛት ወደ ቤትህ እገባለሁ፤ አንተን በመፍራት ወደ ቅድስናህ መቅደስ እሰግዳለሁ።

8 አቤቱ፥ ስለ ጠላቶቼ በጽድቅህ ምራኝ፤ መንገዴን በፊትህ አቅና።

9 በአፋቸው እውነት የለምና፥ ልባቸውም ከንቱ ነው፤ ጕሮሮአቸው የተከፈተ መቃብር ነው፤ በምላሳቸው ይሸነግላሉ።

10 አቤቱ፥ ፍረድባቸው፥ በምክራቸውም ይውደቁ፤ ስለ ክፋታቸውም ብዛት አሳድዳቸው፥ እነርሱ ዐምፀውብሃልና።

11 በአንተ የሚታመኑት ሁሉ ግን ደስ ይላቸዋል፤ ለዘላለሙ ደስ ይላቸዋል፥ እነርሱንም ትጠብቃለህ፤ ስምህንም የሚወድዱ ሁሉ በአንተ ይመካሉ።

12 አንተ ጻድቁን ትባርከዋለህና፤ አቤቱ፥ እንደ ጋሻ በሞገስ ከለልኸን።

መዝሙር 6

ለመዘምራን አለቃ በበገናዎች ስለ ስምንተኛ፤ የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ በቍጣህ አትቅሠፈኝ፥ በመዓትህም አትገሥጸኝ።

2 ድውይ ነኝና አቤቱ፥ ማረኝ፤ አጥንቶቼ ታውከዋልና ፈውሰኝ።

3 ነፍሴም እጅግ ታወከች፤ አንተም አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ነው?

4 አቤቱ፥ ተመለስ ነፍሴንም አድናት፥ ስለ ቸርነትህም አድነኝ።

5 በሞት የሚያስብህ የለምና፥ በሲኦልም የሚያመሰግንህ ማን ነው?

6 በጭንቀቴ ደክሜያለሁ፤ ሌሊቱን ሁሉ አልጋዬን አጥባለሁ፥ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ።

7 ዓይኔ ከቍጡ ዕንባ የተነሣ ታወከች፤ ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ አረጀሁ።

8 ዓመፃን የምታደርጉ ሁሉ፥ ከእኔ ራቁ፥ እግዚአብሔር የልቅሶዬን ቃል ሰምቶአልና።

9 እግዚአብሔር ልመናዬን ሰማኝ፤ እግዚአብሔር ጸሎቴን ተቀበለ።

10 ጠላቶቼ ሁሉ ይፈሩ እጅግም ይጐስቍሉ፤ ወደ ኋላቸው ይመለሱ፥ በፍጥነትም ይፈሩ።

መዝሙር 7

ስለ ብንያማዊ ሰው ስለ ኩዝ ቃል ለእግዚአብሔር የዘመረው የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ አምላኬ፥ በአንተ ታመንሁ፤ ከሚያሳድዱኝ ሁሉ አድነኝና አውጣኝ፥

2 ነፍሴን እንደ አንበሳ ነጥቀው እንዳይሰብሩዋት፥ የሚያድንና የሚታደግ ሳይኖር።

3 አቤቱ አምላኬ፥ እንዲህስ ካደረግሁ፥ ዓመፃም በእጄ ቢኖር፥

4 ክፉ ላደረጉብኝም ክፉን መልሼላቸው ብሆን፥ ጠላቴንም በከንቱ ገፍቼው ብሆን፥

5 ጠላት ነፍሴን ያሳድዳት ያግኛትም፥ ሕይወቴንም በምድር ላይ ይርገጣት፥ ክብሬንም በትቢያ ላይ ያዋርዳት።

6 አቤቱ፥ በመዓትህ ተነሥ፥ በጠላቶቼ ላይ በቍጣ ተነሣባቸው፤ አቤቱ አምላኬ፥ ባዘዝኸው ትእዛዝ ንቃ።

7 የአሕዛብም ጉባኤ ይከብብሃል፥ በእነርሱም ላይ ወደ ከፍታ ተመለስ።

8 እግዚአብሔር በአሕዛብ ይፈርዳል፤ አቤቱ፥ እንደ ጽድቄ ፍረድልኝ፥ እንደ የዋህነቴም ይሁንልኝ።

9 የኃጥኣን ክፋት ይጥፋ፥ ጻድቁን ግን አቅና፤ እግዚአብሔር ልቡናንና ኵላሊትን ይመረምራል።

10 እግዚአብሔር የጽድቅ ጋሻዬ ነው ልበ ቅኖችን የሚያድናቸው።

11 እግዚአብሔር የእውነት ዳኛ ነው፥ ኃይለኛም ታጋሽም ነው፥ ሁልጊዜም አይቈጣም።

12 ባትመለሱ ግን ሰይፉን ይስላል፥ ቀስቱን ገተረ አዘጋጀም፤

13 የሞት መሣርያንም አዘጋጀበት፥ ፍላጻዎቹንም የሚቃጠሉ አደረገ።

14 እነሆ፥ በዓመፃ ተጨነቀ ጉዳትን ፀነሰ ኃጢአትንም ወለደ።

15 ጕድጓድን ማሰ ቈፈረም። ባደረገውም ጕድጓድ ይወድቃል።

16 ጉዳቱ በራሱ ይመለሳል፥ ዓመፃውም በአናቱ ላይ ትወርዳለች።

17 እግዚአብሔርን እንደ ጽድቁ መጠን አመሰግናለሁ፥ ለልዑል እግዚአብሔርም ስም እዘምራለሁ።